በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የዲጅታል የባንክ ሥርዓት በጊዜያዊነት መቋረጥን አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የተሰጠ መግለጫ

በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የዲጅታል የባንክ ሥርዓት በጊዜያዊነት መቋረጥን አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የተሰጠ መግለጫ ***** መጋቢት 7 ቀን 2016 ዓ.ም በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የዲጅታል የባንክ ሥርዓት ላይ ባጋጠመ ችግር ምክንያት የባንኩ መደበኛ አገልግሎቶች ለተወሰኑ ሰዓታት መቋረጣቸዉ ይታወቃል፡፡ እንደሚታወቀው ቀልጣፋና ደህንነቱ የተጠበቀ አገልግሎት ለመስጠት ባንኮች በሥርዓቶቻቸዉ ላይ በየጊዜዉ የደህንነት ፍተሻ እንዲሁም የማሻሻያ ሥራዎችን ያከናዉናሉ፡፡ በሥርዓቶቹ ላይ በሚከናወን ለዉጦችና ፍተሻዎችም የባንኮች አገልግሎት አልፎ አልፎ ሊቋረጥ ይችላል፡፡ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በትናንትናው ዕለት የተከሰተዉ የአገልግሎት መቋረጥ ከዚሁ ጋር የተያያዘ መሆኑን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ለማረጋገጥ ችሏል፡፡ ችግሩ ከተከሰተበት ሰዓት አንስቶ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን የባንኩን እና የደንበኞቹን ደህንነት ለማረጋገጥ ከፍተኛ ክትትል ሲያደርግ ቆይቷል። በመሆኑም የባንኩ መደበኛ አገልግሎቶች በአጭር ጊዜ ዉስጥ እንዲጀምሩና ባንኩ ወደተለመደው እንቅስቃሴው እንዲመለስ ማድረግ ተችሏል፡፡ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ላይ የተከሰተዉ የአገልግሎት መቋረጥ ባንኩ በመደበኛነት በሥርዓቶቹ ላይ በሚያደርገዉ ማሻሻያና ፍተሻ ምክንያት የተከሰተ እንጂ የባንኩን፣ የደንበኞቹን እንዲሁም አጠቃላይ የፋይናንስ ሥርዓቱን አደጋ ላይ የሚጥል ክስተት አለመሆኑን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ለማረጋገጥ ችሏል፡፡ ሙሉውን መግለጫ ይህን ማስፈንጠረያ ይጫኑ https://www.facebook.com/share/p/NfFKPWGURamDzATU/?mibextid=Nif5oz